ስለ አንድነት ብዙ ጊዜ ይወራል ። አንድነት ስንል ግን ምን ማለታችን ነው ? አንድ ላይ እንስራ እና አንድ ሆነን እንስራ በሚሉት ሃሳቦች መሃከል ውስጥስ ያሉትስ ልዩነቶች ምንድን ናቸው ? የአንድነት ኃይሎች ፣ እንደ’ሚታሙት (እንደሚባሉት) ፣ “አንድነት” የሚለውን ሃሳብ ለ -ፖለቲካ ግብዓትነት ነው የሚጠቀሙበት ወይስ የአንድነትን ጥቅም ስለተረዱ ነው ሃሳቡን የሚያቀነቅኑት ? የአንድነት ኃይሎች ስለመሆናቸው ማሳያውስ ምንድን ነው ? አረጓዴ፣ ብጫ እና ቀይ ቀለም ያለው የሀገራችንን ሰንደቅ በመሸከማቸው ? ስለ በላይ ዘለቀ ፣ አሉላ እና ቴዎድሮስ በመስበካቸው ? ስለ ላሊበላ አክሱም እና የሐ በመዝፈናቸው ? አንድነት መገለጫው ምንድን ነው ?
ለምሳሌ እኔ የታዘብኩትን ነገር ላስቀምጥ ። ሕወሓት ከመፈጠሩም -በፊት የትግራይ ሕዝብ በ-አሉላ እና በ-አጼ በዮሃንስ ይሸልል ነበር ፣ ዘፈኖቹ በአብዛኛው የነዚህን ሰዎች ስሞች እየጠቀሱ የሚዘፈኑ ነበሩ ፣ አሁን በጣም ቢመናመኑም አልሞቱም ፣ ዛሬም አሉ ! ወደ ጎንደር ስንወርድ ያለው ነገር ያው ነው ፣ ቴዎድሮስ እና ፋሲል ነው የሚባለው ፣ የልጆቻቸው ስም የሚያንጸባርቀውም እሱኑ ነው ፣ ” ቴዎድሮስ ” ፣ ” ፋሲል” ” ሸዋን ግዛው ” እና ወዘተ ። ወደ ጎጃም ስትሄድ ደሞ ” ድሮም የበላይ ነኝ ” ነው የሚለው ዘፈኑ ። በሚኒሊክ ጀግንነት ላይ አንዳች ልዩነት የሌለው ጎጃሜ ፣ ” ጥንትም የበላይ ነኝ ” ወይም ” “እኔ የበላይ ዘር” ባለበት አንደበቱ ” ጥንትም ያሉላ ነኝ ” ወይም ” እኔ የሚኒልክ ዘር” ብሎ ሲዘፍን አይተን አናውቅም ። ወደ ሸዋም ስትወርድ እንዲሁ ነው ። < አንኮበር የሚኒልክ ሀገር> እየተባለ ይዘፈናል ፣ < ትግራይ የ አሉላ ሀገር > ተብሎ ሸዋ ውስጥ ሲዘፈን የማስታውሰው ነገር የለም ። እኔ እስከማውቀው ድረስ ። ወሎም ከዚህ የተለየ ነገር የለም ፣ የወሎ ሰዎች ስለ ንግስና ሲያወሩ ወይም ሲጫወቱ ዛሬም ስለ ልጅ እያሱ አገዳደል መጫወቱ ይቀላቸዋል ። ተጋዳላዮች ፣ ዛሬም በየ ቡና ቤቱ ስለ ደርግ እንደሚያወሩት ማለት ነው ። የጅማ ኦሮሞዎች ስለ አባ ጅፋር ብዙ ዘፍነዋል ፣ ከጅማ ስለ ሚኒሊክ ፣ በአባ ጅፋር ቅላጼ ፣ ፍቅር መጠበቅ በአሁኑ ሰዓት እጅግ አስቸጋሪ ነው የሚለው ብቻ የሚገልጸው አይመስለኝም። ባሌ-ጎባም እንዲሁ ነው ። ወለጋም ያው ነው ። ይህንን ነባራዊ ሁኔታ በትክክል ለሚያጤን ጤነኛ ሰው፣ < አንድነት ማለት ምን ማለት ነው?> ለሚለው ጉዳይ ትክክለኛ መልስ ይኖረዋል ብዬ አልገምትም ። እንደገባኝ ግን በኢትዮጵያ ታሪክ አንድነት ማለት ስለ ራስ ብቻ እየዘፈኑ ስለ ሌሎችም ያገባኛል ማለት ይመስለኛል ። ከማየው እና ከተረዳሁት ፣ አንድነት ብለን ስንሰብክ ፣ ባንደበታችን ኢትዮጵያዊ ስንሆን በልቦናችን ግን ትግሬ ብቻ ነን ፣ ጎንደሬዎች ብቻ ነን ፣ ጎጃሜዎች ብቻ ነን ፣ ወሎዬዎች ብቻ ነን ፣ የሸዋ ሰው ብቻ ነን ፣ ኦሮሞዎች ብቻ ነን ፣ ጉራጌዎች ብቻ ነን ፣ ሀደሬዎች ብቻ ነን ፣ ዶርዜዎች ብቻ ነን ። ለዚህ ደሞ ብዙ ማሳይዎች አሉ ። ለምሳሌ አንድ የታወቀ ጎጃሜ ሲሞት ፣ መጀመሪያ ለ ጎጃምነቱ ነው ደረት የሚመታው ፣ ኢትዮጵያዊነቱ የሚመጣው ከዚያ ቀጥሎ ነው ። አንድ ጎንደሬ ዘፋኝ ሙዚቃ ሲያወጣ መጀመሪያ ለጎንደሬነቱ ነው ወሬው የሚራገብለት ፣ ኢትዮጵያዊነቱ ሁለተኛ ወይም ሶስተኛ ነገር/ ጉዳይ ነው ። ለኦሮሞውም እንዲሁ ነው ፣ ለሸዋውም ያው ነው ። የትግሬው ትንሽ የተጋነነ የሚመስለው ፣ አደረጃጀቱም ፣ መዋቅሩም ፣ አሰራሩም ሙሉ በሙሉ ዘርን መሰርት ያደረገ ስለሆነ ነው እንጂ እውነቱን ለመናገር ሁሉም አንድ አይነት ነው ። አይንድ አይነት ባይሆን ኖሮ ፣ ትግሬ ብቻውን የተለየ ባህሪ ይዞ መጥቶ ፣ ይህንን ሁሉ ሕዝብ ረግጦ መግዛት ባልቻለ ነበር ።
ለዚህ ነው ጎረምሳ ና ዘረኛ ( ጎሳ ተኮር ) ፖለቲከኞች ፣ ባንድ መንፈቅ –ሺ ተከታዮችን የሚያፈሩት ፣ልባቸው በትዕቢት የሚሞላው እና የሚያብጠውም ፣ የመሃብረሰባችንን ስነ ልቦናዊ የማንነት አወቃቀር በደንብ ስለሚረዱት ይመስለኛል ።
ፖለቲከኞቻችን ( ወይም አሁን ባለው ሁኔታ ቧልተኞቻችን ) ፣ < የጋራ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ > የሚሏት ጥራዝ ነጠቅ አስተሳሰብ አለች ። በመጀመሪያ የጋራ ማለት ምን ማለት ነው ፣ ቁንጽል የጋራ ? ግማሽ የጋራ ? እሩብ የጋራ ? የሚባሉ ነገሮች አሉ ወይ ። የጋራ በሆኑ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ አብረን ለመስራት ተስማምተናል ስንል ፣ አንድ ሞኝ የጋራ ባልሆኑትስ ብሎ ሊጠይቅ ይችላል ። ዋናው ጥያቄ ግን የጋራ የሆኑት ጉዳዮች ፣ የጋራ ከማያረጉን ጋ ሲወዳደሩ ፣ ለጋራ ጉዳዮች አብሮ ከመስራት የጋራ ባልሆኑ ጉዳዮች ላይ መጣላት የተሻለ ሊሆን ይችላል ። ( የተሻለ ነው አላልኩም !)።
ወይም አብሮ መስራቱ ምን ማለት እንደሆነ እንዴት እንዳልገባን ላስረዳ ።
ለምሳሌ ድርጅት ሀ እና ድርጅት ለ የጋራ የሚያደርግ የፖለቲካ ጉዳይ አላቸው እንበል ። ይህም የፖለቲካ ጉዳይ ድርጅት መ’ን ማስወገድ ሊሆን ይችላል ። ግን ድርጅት ሀ የራሱን ክልል መስርቶ መኖር ይፈልጋል ፣ ድርጅት ለ ደሞ ሀገር አንድ አድርጎ ማስተዳደር ይፈልጋል ። ድርጅት ለ ድርጅት መ ወድቆ ድርጅት ሀ የራሱን ክልል ልመስርት ቢል እንቢ ማለት አይችልም ። ምክንያቱም አብረው የሰሩት ድርጅት ሀ የራሱን ክልል እንዳይመሰርት ሳይሆን ድርጅት መ’ን ለመጣል ብቻ ነው ። ከዚህ ባለፈ ብዙ ውስብስብ የሆኑ ጉዳዮች አሉ ። በዘር ላይ የተደራጁ የፖለቲካ ድርጅቶች ትልቅ የሚያደርጋቸውም በዘር መደራጀታቸው ብቻ አይደለም ። ዘረኛ ተከታዮችም ስላሏቸው ጭምር እንጂ ! ለምሳሌ ወጣት መ ብቻውን አንድ ሰው ነው ። መ’ን ትልቅ ያደረገው ግን የሱ አይነት አመለካከት ያላቸው ብዙ ሺዎች ስለሚከተሉት ነው ። ችግር ከተባለ ፣ ችግሩ መ ላይ ሳይሆን፣ የተከታዮቹ ላይ ነው ያለው ማለት ነው ።
ይህንን ሳስብ ነው < አንድ ሆነን አናውቅም አንድ ላይ ግን ኖረን እናውቃለን> ፣ ብዬ ለማለት የምደፍረው ።
የወያኔ ጭካኔ ፣ ዘረኝነት እና ሌሎችም ገልጸን የማንጨርሳቸው ጉዳዮች ዛሬ ሀገራችን ያለችበትን እውነታ ይገልጽ ይሆናል ። ግን እውነታ ስለሆነ ችግሩ ምን እንደሆነ ታውቋል ማለት አይደለም ። ሜርሊን ሮብርሰን ” Fact explains nothing, in the contrary it is fact that requires explanation ” ትላለች ። እውነታ አንዳች የሚገልጸው ነገር የለም ፣ ይልቅስ እውነታው ነው ማብራሪያ የሚያስፈልገው ” እንደማለት ነው ። ጸሓይ ትሞቃለች ( ወይም ታሞቃለች ) እውነታ ነው ፣ እውቀት እና እውነቱ ግን ያለው ለምን ትሞቃለች ( ወይም ታሞቃለች ) የሚለው ላይ ነው ። ወያኔ የሚገዛን አንድ መሆን ባለመቻላችን ነው የሚለው አርፍተ ነገር እውነታ ነው ፣ ለምን አንድ መሆን አቃተን የሚለው ግን እውነታውን የሚያብራራ እውቀት ነው ። ጥያቄው < እንድ እንሁን > አይመስለኝም መሆን ያለበት ፣ ጥያቄም መሆን ያለበት እንዴት አንድ እንሁን የሚለው ላይ ነው ። በዘር ፣ በቋንቋ ፥ በመልካ-ምድር እና ወዘተ መለያየቱ አይመስለኝም አንድ እንዳንሆን ያገደን ፣ ወይም አንድ ከሆንን ወዲያ በአንድነት እንዳንቆም እንከን የሆነብን። ለኔ ችግሩ ያለው የትራክተር ጎማ ፣ የቤቢ ፊያት ኢንጅን ፣ የዔነትሬ ማርሽ አንድ ላይ ገጣጥመን ሀገር የምትባል መኪና ሰርተናል ማለታችን ላይ ነው ። የጋራ የሚያደርጉን ሃሳቦች ሲገጣጠሙ የሚሰሩት የተጣመሙ ነገሮችን ብቻ ነው ፣ ምክንያቱም የቆምንበት መሰረት የኛን ሚዛን ብቻ እንዲሸከም ሆኖ የተሰራ ነውና ።
ታዋቂው ገጣሚ ስፔናዊው አንቶኒዮ ማቼዶ
“wanderer, there is no path,
the path is made by walking.”
the path is made by walking.”
“ኳታኞች፣ ምህዋር የለም
ምህዋር በእርምጃ ነው የሚሰራው !” ይላል ።
ምህዋር በእርምጃ ነው የሚሰራው !” ይላል ።
ስለዚህ ስለ አንድነት ስናወራ
ኳታኞች በመንደርተኝነት መስረት ላይ የቆመ ሀገር የለም !
ሕዝብ ሆይ በፊርማ እና በቅስቀሳ የሚመጣ አንድነት የለም ፣ በስምምነት እና በወረቀት የሚገኝ ህብረተሰባዊነት የለም ፣ አንድነት አብሮ በመኖር ነው የሚመጣው ፣ እሱን ለማምጣት መጀመሪያ ራሳችንን ከራስችን ውስጥ ማስወጣት !
No comments:
Post a Comment